Thursday, November 5, 2015

ፍፁም ቅዱሷ ሃጥዓተኛ

ከሜሮን ጋር ሻይ ቡና እያልን ስለመንፈሳዊነት (mysticism) ስናወጋ መግደላዊት ማሪያም ተነሳች። “ካች ዩር ተንደር” በህትመት ሂደት ላይ ነበር ያኔ። ከረቂቁ ላይ ይህችን ቅድስት የሚያነሳን ኣንድ ምዕራፍ ኣነበብኩላት። (ከታች በስዕሉ ላይ የጠቀስኩትን።) በሌላ ጊዜ ስንገናኝ ሜሮን “የመግደላዊት ማሪያም ወንጌል“ (በእንግሊዝኛ) የሚለውን የJean-Yves Leloup መፅሃፍ ኣዋሰችኝ። እንዲህ በቀላሉ ኣገኘዋለሁ ብዬ ያላሰብኩት መፅሃፍ ነበር። “ተባረኪ ኣቦ!” ብዬ ተቀበልኳት። መፅሃፉን ሳነብበው ስለመግደላዊት ማሪያምም ሆነ ስለክርስትና ኣላውቃቸው የነበሩ ብዙ ነገሮችን ኣገኘሁበት። ይህ ክርስትና ብዙዎቻችን ከምናስበው ውጪ ብዙ ድብቅ ታሪኮች እንዳሉት እና ኢየሱስ ያስተማረው ክርስትና እኛ ጋ ሙሉ በሙሉ እንዳልደረሰ ከሚያሳዩ መፅሃፍት ኣንዱ መሆኑ ነው። “ፍፁም ቅዱሷ ሃጥዓተኛ“ የሚለው ሃሳብ ይህንን መፅሃፍ ከማንበቤ በፊት የነበረኝ ዕይታ ነበር። ኣሁን ግን ሃጥዓተኛነትን ከመግደላዊት ማሪያም ጋር ኣገናኝቶ ማሰብም ራሱ “ይቅር በለኝ!“ የሚያስብል እንደሁ ተረድቻለሁ። (እዚህ በተለይ በክርስትና ተረክ ተፅዕኖ የተበጀውን የቀድሞ ዕይታዬን ለማሳየት ብቻ ተጠቀምኩበት።) በሚቀጥሉት ጦማሮቼ ከጠቀስኩላችሁ መፅሃፍ ያገኘሁዋቸውን ኣንዳንድ ነገሮች ወደኣማርኛ መልሼ ላጋራችሁ ተዘጋጅቻለሁና ተጋበዙ፣ ተገባበዙልኝ። እተረጉመው ዘንድ የስህን (ዶ/ር) ቀና ግፊት ጉልበት ሆኖኛልና ለሜሮንና ለእርሷ ምስጋና!

No comments:

Post a Comment